ከህዝባዊ መብት መሻር የምስክርነት ቃል ከመስጠት አንጻር ያለው እንድምታ (implication of deprivation from civil rights)
አንድ በወንጀል ተጠርጥሮ የጥፋተኝነት ፍርድ የተሰጠበት ሰው በጽኑ እስራት ከተቀጣ ከህዝባዊ መብቱ ጭምር እንዲሻር በ1996 ዓ.ም በወጣው የኢፌድሪ የወንጀል ህግ አንቀጽ 123 ላይ በአስገዳጅነት ተደንግጎ ይገኛል፡፡ አንድ በጽኑ እስራት የተቀጣ ሰው ከህዝባዊ መብቱ ተሽሯል የሚባለው ከምን አይነት ህጋዊ ተግባራት ነው የሚለው ነጥብ ከዚህ በላይ በተጠቀሰው ድንጋጌ ላይ ተመላክቶ ይገኛል፡፡ ከህዝባዊ መብት መሻር በሚለው የወንጀል ህግ ቁጥር 123 (ሀ) ላይ የተሰረዘሩት ከመራጭነት መብት፣ በአንድ ምርጫ ተካፋይ ከመሆን እና ለህዝብ አገልግሎት ከመመረጥ ፣ ወይም ለማዕረግ ከመመረጥ፣ በሰነድ ወይም የውል ስምምነት ላይ ምስክር ወይም ዋስ ከመሆን፣ ለፍርድ ስራ ልዩ አዋቂ ወይም ነባሪ ሆኖ ከመስራት መሻርን ያጠቃልላል፡፡ በወንጀል ህግ ያልተማለከቱ ፍሬ ነገሮች በትርጉም በመውሰድ ተግባራዊ ማድረግ እንደማይቻል ከወንጀል ህግ ልዩ ባህሪ ወይም የህጋዊነት መርህ እንድምታ አንጻር መመልከት ይገባል፡፡
በአሰራር አንዳንድ ጉዳዩች ላይ ተከሳሹ በጽኑ እስራት ሲቀጣ ከህዝባዊ መብት የማይሻርበት ሁኔታ ይታያል፡፡ ይህ አሰራር ከዚህ በላይ በአስገዳጅነት ከተመላከተው ድንጋጌ አንጻር ተገቢነት የለውም፡፡ ከህዝባዊ መብቶች መሻር ጋር ተያይዞ የሚነሳው አከራካሪ ጉዳይ “ -------- አንድ በጽኑ እስራት የተቀጣ ሰው በፍርድ ቤት ቀርቦ ከመመስከር ሙሉ በሙሉ ሊታገድ ይገባል ወይ ?------” የሚለው ነጥብ ነው፡፡
አንዳንድ የሕግ ባለሙያዎች በአንቀጽ 123(ሀ) ስር ከተመለከቱት የሕጉ ፍሬ ነገሮች ውስጥ ----ለፍርድ ስራ ልዩ አዋቂ ወይም ነባሪ--- ከመሆን የሚለው ሀረግ በጥቅሉ በጽኑ እስራት ተቀጥቶ ከህዝባዊ መብቶቹ የተሻረ ሰው በምንም መልኩ በፍርድ ቤት ቀርቦ የምስክርነት ቃሉን ሊሰጥ አይገባም በማለት ይከራከራሉ፡፡
ሌሎቹ የሕግ ባለሙያዎች ደግሞ አንድ በጽኑ እስራት ተቀጥቶ ከህዝባዊ መብቶቹ የተሻረ ሰው ጥፋተኛ የተባለበትን የወንጀል ድርጊቱን ከመፈጸሙ በፊት የሚያውቃቸውን ሁኔቶች ከመመስከር ህጉ አይከለክለውም፡፡ ምክንያቱም ይህ ጥፋተኛ የተባለው ሰው ስለ ሌሎች ሰዎች የወንጀል ድርጊቱን ከመፈጸሙ በፊት የሚያውቃቸውን ሁነቶች እንዳይመሰክር መከልከል ከእርሱ ይልቅ የሌሎች ሶስተኛ ሰዎች መብቶች እንዲጣሱ ያደርጋል በማለት መከራከሪ ያነሳሉ፡፡
ፀሀፊው በሁለተኛ ደረጃ የተጠቀሱት የህግ ባለሙያዎች የሚያነሱትን መከራከሪያ ነጥብ ተገቢነት ያለው ነው ብሎ ያምናል፡፡ ለዚህም መሰረቱ የድንጋጌው ይዘት ነው፡፡ የድንጋጌው የእንግሊዝኛ ቅጂ “----to be an expert witness or to serve as assessor----“ በሚል የተገለፀው ሀረግ በራሱ በጽኑ እስራት የተቀጣው ሰው የተከለከለው ለፍርድ ልዩ ስራ አዋቂ ወይም ነባሪ ለማመልከት እንጂ ተከሳሹ በጽኑ እስራት ከተቀጣ በፍጽም በፍርድ ቤት ቀርቦ የምስክርነት ቃሉን ከመስጠት ይከለከላል ለማለት ባለመሆኑ የተነሳ ነው፡፡ ለዚህ ክርክር አንድ ማሳያ ብንወስድ በጽኑ እስራት ተቀጥቶ ከህዝባዊ መብቶቹ የተሻረ ሰው ጥፋተኝ የተባለበትን የወንጀል ድርጊት ከመፈጸሙ በፊት በአንድ የኑዛዜ ቃል ላይ እማኝ ቢሆን አና ከዚህ ሰው ውጪ ያሉት በኑዛዜው ላይ ያሉት ሰዎች በህይወት ከሌሉ በኑዛዜው መሰረት ክርክር የሚያቀርብ ሰው በማስረጃነት አያይዞ ያቀረበው በጽኑ እስራት ተቀጥቶ ከህዝባዊ መብቱ የተሻረውን ሰው እና የኑዛዜ ሰነዱን ቢሆን ምስክሩ ከህዝባዊ መብቱ ስለተሻረ የምስክርነት ቃሉን አይደጥም ቢባል በኑዛዜ መሰረት መከራካሪያ ያቀረበው ግለሰብ መብት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ በወንጀል ጉዳይ ላይ ጥፋተኛ የተባለ ሰው በሌሎች ሰዎች መብት ላይ ተፅዕኖ እንዳይኖረው ማድረግ የግድ የሚል ነው፡፡ ሌላ ምሳሌ እንመልከት አንድ በወንጀል ተጠርጥሮ ክስ የቀረበበት ሰው የተጠረጠረበት የወንጀል ድርጊት ላለመፈጸሙ የሚዉቁለት ሁለት ሰዎች ብቻ ቢሆኑ እና እነዚህ ሁለት ሰዎች ይህ ክስ የቀረበበት ሰው ክስ ሳይቀርብበት በጽኑ እስራት ተቀጥተው ከህዝባዊ መብታቸው ተሽረው ማረሚያ ቤት የሚገኙ ቢሆን ከህዝባዊ መብታችሁ ስለተሻራችሁ ምስክር መሆን አትችሉም የሚባል ከሆነ የተጠርጣሪውን መከላከያ አቅርቦ የማሰማት ህገ መንግስታዊ መብቱን የመንፈግ ያህል ይቆጠራል፡፡ በመሆኑም አንድ በጽኑ እስራት ተቀጥቶ ከህዝባዊ መብቱ የተሻረው ሰው በምንም መልኩ በፍርድ ቤት ምስክር ሆኖ ሊቀርብ አይችልም የሚለው ከድንጋጌው ይዘት አንጻር አግባብነት የለውም፡፡
እርስዎ የትኛውን መከራከሪያ ሀሳብ ይደግፋሉ?
Негізгі бет በጽኑ እስራት የተቀጣ ሰው ከህዝባዊ መብቱ ሲታገድ ታራሚው የአይን ምስክር ከመሆን ይከለከላል ወይ?
Пікірлер