ሃገሬ
የገፅታሽን ግርማ የሚገልፀው ስምሽ
በፈሪሃ እግዚያብሄር የተሞላው ገድልሽ
በእምነት መፅሃፍት በእኩል ተፅፈዋል
ቀድምትነትሽን ለአለም መስክረዋል
እናቴ
በዛፍ ስር ቁጭ ብለው
ከሳሽ ተከሳሹን በጥሞና አድምጠው
በሀቅ የሚፈርዱ አባይ ያልነበሩ
ለእውነት የቆሙ አባቶች ነበሩ
የወለዱትን ልጅ ከመንደሩ ልጆች ሳያበላልጡ
እናቶች ነበሩ በእኩል የሚቀጡ
ትጉህ ሰራተኞች የዘመመውን ቤት በትጋት ያቀኑ
ባለ እናት አንጀቶች ለአደራ የታመኑ
ሰው አየ አላየ ግድ ያልነበራቸው
ታዛዥ የነበሩ ለህገ ህሊናቸው
ረዳት ነበሩ
ግፍን የሚፈሩ
በስልጣኔ ቀደምት በለምለሟ ሃገር
ሃይማኖት ሳይለየው ዘር ቀለም ሳይቆጥር
ደሃ ሃብታም ሳይል ተሳስቦ ተዋዶ ህዝብሽ ይኖር ነበር
ሃገሬ
ዛሬ ግን እናቴ ሃገሬ ዛሬ ግን
ጆሮን ጭው የሚያደርግ የሚያደማ ልብን
ትናጋ የሚያጣብቅ እጅ በአፍ የሚያስጭን
አይናችን ጠገበ ዝናሽ ሆኖ ሰማን
የጭካኔ ቁንጮ የክፋት ሁሉ ጥግ
ፍቅር ካንቺ ርቆ ተናፍቆ ፍትህ ህግ
ወገን ለወገኑ ለሴት ወንድ ሳይራራ
ነፍሰጡር ሲበልት ህፃን ሲያርድ በካራ
አስክሬን ከምሮ ሲጨፍር ሲያቅራራ
አባት ልጁን ደፍሮ እናት በአባት ሃፍረት ለሰሚው ተጨንቃ
አዩ አላዩ ብላ ለልጇ ተሳቃ
እንቦቀቅላዎች አደራ በበሉ በጨካኝ እጅ ታርደው
ወላድ እያነባ በእንብርክክ የሄደው
ግፍ በደል ጭካኔ አመፅ ዘረኝነት በተንሰራፋበት ኢትዮጵያ ባንቺ ነው
ሃገሬ
አሁን ግን ይህ በቃሽ
በቃ ይብቃሽ
ዛሬ ልመርቅሽ ሃገሬ ልባርክሽ
ዘመንሽ ሲለወጥ ይህን አዲስ አመት አንድ ብለሽ ስትቆጥሪ
ሰላምን ፍቅርን ለአለም አብስሪ
መፍትሄ ካንቺ ይገኝ በኪዳን ቃል አብሪ
ሃገሬ
ይውደድሽ የሚያይሽ
ይጣፍጥ ንግግርሽ
ፍርድሽ በእውነት ይሁን ህግሽም የጸና
እንባ ከአይን ይታበስ ጠማማው ይቃና
ሃገሬ
ከሰሜን ከደቡብ ከምስራቅ ከምእራብ ልጆችሽ ይስማሙ
ከያሉበት ቦታ ለአንድነት ይትመሙ
ለእርቅ ለይቅርታ ይከፈት ልባቸው
ጠላታችን ይፈር ቃል ይሁን ጦራቸው
ቃል
የሚያፈራ የሚበቅል
ቃል የሰላም ቃል የፍቅር
ደረቅ መሬት አለምልሞ የሚነቅል ክፉውን ዘር
ሃገሬ
ለጥፋት የፈጠነ ጭንቅላት ወደ ሞት የሚሮጥ እግር
ክፉ ሃሳብ የሚያበቅል ልብ በሃሰት የሚናገር ምስክር
ጠማማ ቃል ወላዋይ ውል ከአንቺ አይገኝ በአንቺ አይኑር
የጉያ እሳት የሃጥአን መንገድ
ከምድርሽ ከአየርሽ ይጥፋ ለዘላለም ይወገድ
ሃገሬ
ህግሽ በእውነት ይሞላ አካሄድሽ ይፅና
ፍሬአማ ይሁን ቀዬሽ መንገድሽም ይቅና
ድርቀት ካንቺ ይራቅ ብሩክ ይሁን ምንጭሽ
ቀላያት በበረከት ይቀደዱ ጠል ያንጠብጥብ ደመናሽ
ጥንቃቄ ይጠብቅሽ ማስተዋልም ይጋርድሽ
ከፍታሽን ውረሺ የእጆችሽ ስራ ይባረኩ
ዜናዎችሽ ለምድር ነገድ የምስራችን ይስበኩ
ትውልድሽ በምህረት በፅድቅ እውነት ይሞላ
ከመሬትሽ አይብቀል እንክርዳድና አሜኬላ
በሞገስ ተጥለቅለቂ አደባባዮችሽ በጥበብ ቃል ይሞሉ
ማቅሽ ከላይሽ ይገፈፍ ያለቀሱ እልል ይበሉ
ሃገሬ
በዚህ በአዲስ አመት በጸሎት አጥብቄ
ለሃገሬ የምመኘው ተስፋዬን ሰንቄ
የሗላሽን ክፉ ጥለሽ አሽቀንጥረሽ
ስታበሪ ማየት ነው በከፍታሽ ቆመሽ
ዛሬ ልመርቅሽ ሃገሬ ልባርክሽ
ይህን አዲስ አመት አንድ ብለሽ ስትቆጥሪ
ለሰው ልጆች ሁሉ ሰላምን ዘምሪ
መፍትሄ ካንቺ ይገኝ በኪዳን ቃል አብሪ
................//...............።
እንኳን ለአዲስ አመት አደረሰን
እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ምድርን ሁሉ ይባርክ! ሰላም ለሰው ልጆች ሁሉ ይሁን!
አሜን!
መስከረም /2015
ሜሊ ተስፋዬ
Негізгі бет ''ሃገሬ'' ግጥም በሜሊ ተስፋዬ
Пікірлер: 9