ቅድስት ቤተ-ክርስቲያን ለምዕመኑ ምኑ ናት?!
ቅድስት ቤተክርስቲያን ለምዕመኑ ምን ማለት እንደሆነች የመንግሥት አካላት በፍጹም የምታውቁ አይመስለኝም፡፡ እናንተ ቅድስት ቤተ-ክርስቲያንን እንደ አንድ «ተቋም» ብቻ ትመለከቷት ይሆናል፡፡ ትልቁን የስሌት ስህተት የሠራችሁት እዚህ ጋር ነው፡፡ ለመሆኑ በ 40 እና 80 ቀናች የሥላሴን ልጅነት ያገኘንባት ፣ የታሪክን ሸማ የለበስንባት፣ በሥነምግባር ያደግንባት ፣ ሰውን ማክበር ሀገርን መውደድ የተማርንባት ዛሬ ግን ዛሬ በፈተና ላይ ያለችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ለእያንዳንዱ የእምነቱ ተከታይ ምዕመናን ምኑ ናት?!
ቅድስት ቤተክርስቲያን ማለት ለምዕመኑ በምድር ያለች የእግዚአብሔር መንግስት ናት፡፡ ቅድስት ቤተክርስቲያን ማለት ለምዕመኑ ከውልደቱ ጀምሮ እስከ ሞቱ ድረስ የማትለየው እና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚገባባት በሩ ናት፡፡ አንድ ሕጻን ከተወለደ በኋላ በአርባ ወይም በሰማኒያ ቀን ጥምቀትን ትፈጽማለች፡፡ ከዚህ በኋላ በየጊዜው የጌታችንን እውነተኛ ሥጋ እና ደም እየመገበች ታንጸዋለች፡፡ እድሜው ለእውቀት ከደረሰ ጊዜ ጀምሮ ደግሞ እውቀትን እየሠጠች ታሳድገዋለች፡፡ ምዕመኑ ቢደሰት ከቤተክርስቲያን ሄዶ ‹እግዚአብሔር ይመስገን› ብሎ ደስታውን ይገልጻል፤ ቢያዝን ደግሞ ከቤተክርስቲያን ሄዶ እያለቀሰ አቤቱታውን ያቀርባል፡፡ በአንድ ነገር ቢበሳጭ ሄዶ የሚረጋጋባት፣ በኃጢአት ቢቆሽሽ ሄዶ ንስሃ ገብቶ እንደ በረዶ ንጹህ የሚሆንባት ቤቱ ናት፡፡ ምዕመኑ በሞት ሲለይ ስንኳ ቤተክርስቲያን አትለየውም፡፡ ቤተሰቦቹን አጽናንታ፤ ለእርሱ ደግሞ ጸሎተ ፍትሐት አድርጋ ትሸኘዋለች፡፡ ምዕመኑን ያለ ቤተክርስቲያንን ኑር ማለት ‹አየር ሳትተነፍስ ኑር› እንደማለት ያለ ቀልድ ነው፡፡
ለዚህ ሲባል መክፈል ያለበትን መስዋእትነት ሁሉ እንደሚከፍል አልገባችሁም፡፡ ምዕመኑን በቤተክርስቲያኑ ምክንያት ብታስሩት ክብሩ ነው፤ ለእርሱ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ካሉት ጋር እየደመራችሁት ነውና፡፡ ምዕመኑን በቤተክርስቲያኑ ምክንያት ብታሰቃዩትም ሆነ ብትገድሉት ክብሩ ነው፤ ለእርሱ እንደ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ቅድስት አርሴማ ካሉ ሰማዕታት ጋር እየደመራችሁት ነውና፡፡
ይህ ምዕመን ያለ ፍርሃት እሥር እና ሞትን ሲጋፈጥ ብታየት አትደነቁ፤ እናንተ ቤተክርስቲያን ለእርሱ ምን ማለት እንደሆነች ስላልገባችሁ ነው፡፡ ልጅ ቢወልድ ጥምቀት የምትፈጽምለትን፣ በንስሃ ኃጢያቱን የምታጥብለትን፣ በክርስቶስ ሥጋ እና ደም የምታከብረውን፣ ቢሞት ስንኳ በክብር የምትሸኘውን ታላቂቱን ቤተክርስቲያን ከነካችሁ ማንም ወደኋላ እንደማይል ጠንቅቃችሁ እወቁ፡፡
ልብ በሉ፤ እስከዛሬ ድረስ በቤተክርስቲያን ላይ መከራ ያጸኑ ብዙ ነበሩ፡፡ ሁሉም ስማቸውን ብቻ ትተው አልፈዋል፤ አጠፋናት ብለው የነበረችው ቤተክርስቲያን ግን ዛሬም አለች፡፡ ይህንን የታሪክ ሐቅ አይታችሁ በጊዜ ተመከሩ፡፡
#አንዲት_ቤተ_ክርስቲያን
#አንድ_ሲኖዶስ
#አንድ_ፓትርያርክ
#eotc_one_holy_synod
#one_church
#one_patriarch
Subscribe 👇 Our KZitem Channel
ዩቲዩብ= / @tobiyamedia
እምነት፣ እውነት፣ እውቀት፣ ጥበብ፣ ፍቅር ሰውን ነጻ ያወጣሉ !
#ጦቢያሚዲያ #TobiyaMedia
© ጦቢያ ሚዲያ
Негізгі бет ቅድስት ቤተ-ክርስቲያን ለምዕመኑ ምኑ ናት ?
Пікірлер