💗 ቅዱሳን ቆዽርያኖስ እና ዮስቴና 💗
ቆዽርያኖስ ማለት አገር ያስጨነቀ የሶርያ ጠንቅ ዋይ (መተተኛ) የነበረ ሰው ነው:: ከሥራዩ ብዛት የተነሳ አጋንንትን የሚፈልገውን ያዛቸው ነበር:: በዚያ ሰሞን ታዲያ ወደ #አንጾኪያ ሔዶ የለመደውን ሊሠራ አሰበ:: እንዳሰበውም ሔደ::
በአንጾኪያ ደግሞ ስም አጠራሯ የከበረ: ክርስትናዋ የሠመረ: ድንግልናዋ የተመሠከረና ደም ግባቷ ያማረ አንዲት ወጣት ነበረች:: ስሟም #ዮስቴና(የሴቶች እመቤት) ይባላል:: እንዲህ ነው ስምና ሥራ ሲገጣጠሙ::
በወቅቱ ደግሞ የእርሷ ጐረቤት የሆነ አንድ ሰው በቁንጅናዋ ተማርኮ 'ላግባሽ' ቢላት 'አይሆንም' አለችው:: ምክንያቱም እርሷ መናኝ ናትና:: በጥያቄ አልሳካልህ ቢለው በሃብት ሊያታልላት: 'እገድልሻለሁ' ብሎ ሊያስፈራራት: በሥራይ (በመስተፋቅር) ሊያጠምዳት ሞከረ::
ነገር ግን አልተሳካለትም:: ምክንያቱም ሟርት በእሥራኤል ላይ አይሠራምና:: በመጨረሻ ግን ወደ #ቆዽርያኖስ ሔዶ "አንድ በለኝ" አለው:: ቆዽርያኖስም "ይሔማ በጣም ቀላል ነው" ብሎ ወዲያው አጋንንትን ጠራቸው:: "ሒዳችሁ ያችን ወጣት አምጡልኝ" ሲልም ላካቸው::
አጋንንቱ ወደ ቅድስት ዮስቴና ሲሔዱ ግን #መላእክት ወርደው ቤቷን በእሳት አጥረውታል:: ተመልሰው "አልቻልንም" አሉት:: እርሱም "አንዲት ሴት ካሸነፈቻችሁማ እኔም ክርስቲያን እሆናለሁ" ብሎ አስፈራራቸው:: አጋንንቱም በማታለል አንዱ ሰይጣን እርሷን መስሎ ሌሎቹ ደግሞ አስረውት መጡ::
ቆዽርያኖስ ይህን ሲያይ ደስ ብሎት "ሠናይ ምጽአትኪ ኦ ዮስቴና እግዝእቶን ለአንስት - የሴቶች እመቤት ዮስቴና እንኩዋን ደህና መጣሽ" ሲል: ስሟ ገና ሲጠራ ደንግጠው አጋንንት እንደ ጢስ ተበተኑ::
"ለዛቲ ቅድስት በኀበ ጸውዑ ስማ:
ከመ እንተ ጢስ ተዘርወ መስቴማ" እንዳለ መጽሐፍ::
ቆዽርያኖስም በሆነው ነገር ተገርሞ "ስሟን ሲጠሩ እንዲህ የራዱ ወደ እርሷማ እንዴት ይቀርባሉ" ብሎ ተነሳ:: መጽሐፈ ሥራዩን በሙሉ አቃጠለ:: ሃብቱንም ለነዳያን አካፍሎ ሒዶ #ክርስቲያን ሆነ:: የሚገርመው ድንግል ነበርና ከብዙ ተጋድሎ በሁዋላ ዲቁናና ቅስናን ተሾመ::
አምላክ መርጦታልና የቅርጣግና (Tunisia) ዻዻስ ሆኖ ተመርጦ የክርስቶስን መንጋ በትጋት ጠብቁዋል:: ቅድስት ዮስቴናም ገዳም አንጻ: ደናግሉን ሰብስባ ንጽሕናን ስታስተምር ኑራለች:: በመጨረሻም መስከረም 21 ንጉሡ ዳኬዎስ ክርስቶስን ካልካዳችሁ በሚል ብዙ አሰቃይቶ አንገታቸውን አሰይፏል::
ቸር አምላክ በኃይለ መስቀሉ ሃገራችንን ከክፉው ሁሉ ይጠብቅልን:: የቅዱሳኑን ጸጋ ክብርም አይንሳን:: አሜን
ምንጭ ››› "ገድለ ቅዱሳን Gedle Kidusan Acts of Saints" የፌስቡክ ገፅ የተወሰደ
አዘጋጅተው ላቀረቡልን ቃለ ሕይወትን ያሰማልን፡፡ አሜን
Негізгі бет ቅድስት ዮስቲና እና ቅዱስ ቆጵርያኖስ - ክፍል 2 / Saints Justina and Cyprian - Part 2 - Ye Kidusan Tarik
Пікірлер: 937