Background Music: • Best Ethiopian Instrum...
የአድዋ ጦርነት የመጀመርያ የኢትዮ-ጣልያን ጦርነት ክፍል ነው። የኢትዮጵያ ጦር የጣልያንን ወራሪ ጦር በእሑድ ዕለት በየካቲት 23 ቀን በ1888 ዓ.ም ለአድዋ ከተማ ቅርብ የሆነ ቦታ ላይ አሸንፎታል። ይህ ወሳኝ ድልም የጣልያን ግዛት በአፍሪካ ቀንድ ቀኝ ግዛቷን ለማስፋፋት ያደረገችን ዘመቻ ያገደ ነበረ። ከበርሊን ስብሰባ በኋላ በ19ነኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻ የአውሮፓ ኃይሎች አፍሪካን ሙሉ በሙሉ ማለት በሚቻል ሁኔታ ተከፋፍለዋት ነበር፤ ራሳቸውን ችለው የቆሙትም ኢትዮጵያና ላይቤርያ ብቻ ነበሩ። አድዋ በፓን አፍሪካኒዝም ውስጥ ታዋቂ ሆነ፤ ከአርባ ዓመት በኋላ እስከመጣው እስከ ሁለተኛው የኢትዮ-ጣልያን ጦርነትም ድረስ የኢትዮጵያ ሉዓላዊነትን አስጠበቀ።
አስቀድመው የሸዋው ንጉስ ምኒልክ ከጣልያኖች ጋር የውጫሌን ስምምነት ተፈራርመው ነበር። ስምምነቱ የተፈረመው ጣልያን ኤርትራን ከያዘች በኋላ ነው፤ በስምምነቱም ኤርትራ የጣልያን እንደሆነች ተስማሙ። በዛም ጣልያን ለኢትዮጵያ የገንዘብና የጦር መሳርያዎች ድጋፍ ለማቅረብ ተስማማች። ኋላ ላይ ግን ሰነዱ በተፃፈበት ሁለት ቋንቋ ትርጉም ልዩነት ምክንያት ግጭት ተነሳ። በጣልያንኛ በተፃፈው የውጫሌ ስምምነት ውስጥ አንቀጽ 17 ላይ እንደሚለው ከሆነ የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ሁሉንም የውጭ ጉዳዮቻቸውን በጣልያን ባለ ሥልጣናት በኩል እንዲያካሂዱ ያስገድዳል። ይህም ኢትዮጵያን በጣልያን ሞግዚትነት ሥር የምትተዳደር ሀገር አደረጋት። በአማርኛ በተፃፈው የውጫሌ ስምምነት ውስጥ ደግሞ አንቀጽ 17 ላይ እንደሚለው ከሆነ ንጉሰ ነገስቱ ከፈለጉ የውጭ ግንኙነቶቻቸውን ለማካሄድ በጣልያን ግዛት የሚገኙ ጥሩ ባለ ሥልጣናትን በመጠቀም ማካሄድ ይችላሉ።
የጣልያን መንግስትም ወታደራዊ ኃይልን በመጠቀም ኢትዮጵያ በግድ በጣልያንኛ የተፃፈውን የውጫሌ ስምምነት እንድትቀበል ለማድረግ ወሰነ። በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያና ጣልያን ፊት ለፊት ተጋፈጡ፤ ይህም ኋላ ላይ የመጀመርያው የኢትዮ-ጣልያን ጦርነት ተብሎ ይታወቃል። የጣልያን ሠራዊትም የትግራይ ዋና ከተማ አድዋን ተቆጣጠሩ። ከወር በኋላም የባራቴሪ ሠራዊት በኮቲት ጦርነት የራስ መንገሻን ጦር በማሸነፍ መንገሻን ወደ ደቡብ እንዲሸሽ አስገደደው።
በ1888 ጣልያኖች የኢትዮጵያን ድንበር አልፈው ጠልቀው ገቡ። በአምባ አላጊ ጦርነትም ራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል፣ ፊት አውራሪ ገበየሁ እና ራስ መንገሻ ዮሐንስ የኢትዮጵያን በቁጥር በላጩን የምኒልክን ግምባር ቀደም የሠራዊት ቡድን በመምራት ትንሹን የጣልያን ጦር ደመሰሱ። ጣልያኖችም በትግራይ ክፍለ ሀገር ራስን ለመከላከል ወደሚመቹ አካባቢዎች መሸሽ ግድ ሆነባቸው።
በየካቲት 22፤ 1888 ባራቴሪ አዲስ ገዥ በሆነው በጄነራል ባልዲስራ ሊቀየር ሲል የጦር መሪዎቹ የነበሩትን ማቴዎ አልቤርቶ፣ ጉሲፒ አሪሞንዲ፣ ቪቶርዮ ዳቦርሚዳ እና ጉሲፒ ኤሌናን አግኝቶ ስለቀጣዩ ደረጃ አዋያቸው። ባራቴሪም የመጨረሻ ደቂቃ መረጃ ስለሚያስፈልገኝ ልጠብቅ በሚል ውሳኔ ለመወሰን ጥቂት ተጨማሪ ሰዓታት ፈጀበት፤ ነገር ግን በመጨረሻ ለወታደሮቹ ማጥቃታቸውን በቀጣዩ ቀን ከጠዋቱ 3:00 እንደሚጀምሩ አሳወቀ። እኩለ ሌሊቱ እንዳለፈ ወድያውኑ የባራቴሪ ሠራዊት ወደ መነሻ ነጥባቸው ዘመቱ።
በምኒልክ ሥር ያለው የሠራዊት ቁጥር በግልፅ ባይታወቅም ከ73000-100000 ነበር፤ የጣልያን ሠራዊትንም በ5 እጥፍ ይበልጥ ነበር። ሠራዊቱም በአፄ ምኒልክ፣ በእቴጌ ጣይቱ ብጡል፣ በራስ ዋሌ ብጡል፣ በራስ መንገሻ አትከም፣ በራስ መንገሻ ዮሐንስ፣ በራስ አሉላ እንግዳ(አባ ነጋ)፣ በወሎው ራስ ሚካኤል፣ በራስ መኮንን ወልደ ሚካኤል፣ በፊት አውራሪ ሐብተ ጊዮርጊስ፣ በፊት አውራሪ ገበየሁ እና በንጉስ ተክለ ሐይማኖት ተሰማ ሥር የተከፋፈለ ነበር። በተጨማሪም ለክፍለ ዘመናት ሲደረግ እንደነበረው ሠራዊቱ በቁጥር ከእነርሱ እኩል በሚሆኑ አቅራቢዎች እየተከተለ ነበር የተጓዘው።
ከአድዋ ጦርነት ጥቂት ቀደም ብሎ የጣልያን ሠራዊት በ29700 ጣልያናውያን እና በ14000 አስካሪዎች የተዋቀረ ነበር። ነገር ግን ሐሮልድ ማርክስ እንዳለው ብዙ ሺህ ወታደሮች ለድጋፍ ሚና እና በኋላ በኩል የነበረውን የግንኙነት መስመር ለመጠበቅ ተፈልገው ነበር። እንዲህም ብሎ በአድዋ የተሳተፉት የጣልያን ወታደሮች ቁጥር 14519 ብቻ እንደሆኑ ተናግሯል። ነገር ግን ዴቪድ ኤል. ሊውስ የጣልያን ሠራዊት አራት ብርጋዴዎች በመያዝ 17770 ሠራዊት እና 56 ከባድ መሳርያን የያዘ ነበር። በጄነራል አልቤርቶን ስር የነበረ አንድ ብርጋዴ በጣልያን ወታደሮች በሚመሩ የኤርትራ አስካሪዎች የተዋቀረ ነበር። የተቀሩት ሦስት ብርጋዴዎች ደግሞ በጣልያን ሠራዊት የተዋቀረ ሲሆን የነበሩት ዳቦርሚዳ፣ ኤሌና እና አሪሞንዲ በተባሉ ብርጋዴሮች ስር ነበሩ። እነዚህም ቁንጮ የሆኑትን የቤርሳግሌሪ እና አልፊኒ ሠራዊትን የያዙ ሲሆን አብዛኛው የሠራዊቱ ክፋይ ልምድ የሌላቸው በግድ ከትልቅ ከተማ የተመለመሉና ወደ አፍሪካ የተላኩ ወታደሮች ናቸው። በተጨማሪም ጥቂት ቁጥር ያላቸው ወታደሮች በአፍሪካ ውስጥ በቋሚነት የሚያገለግሉ እና ከጣልያን ሰፋሪዎች የተመለመሉ ነበሩ።
በየካቲት 22 ምሽትና በየካቲት 23 ንጋት ሦስት የጣልያን ብርጋዴዎች ተከፋፍለው በጠባብ የተራራ መንገዶች በኩል ወደ አድዋ አቀኑ፤ 4ተኛው ብርጋዴም በሰፈረበት ተቀመጠ።
የራስ አሉላ ሰላዮችም ጣልያኖች እየቀረቡ እንደሆነ ዜናውን ለንጉሰ ነገስቱ ባመጡ ጊዜ ንጉሰ ነገስቱ መለኮታዊ መሪነት ለማግኘት በጠዋቱ ጸሎት ለመጀመር ነቅተው ነበር። ንጉሰ ነገስቱም ሠራዊታቸውን ወደፊት እንዲጓዙ አዘዙ። ንጉስ ተክለ ሐይማኖትም የቀኙን መስመር፣ ራስ መንገሻም የግራውን መስመር፣ ራስ መኮንንም የማዕከሉን እና ራስ ሚካኤልም የላዩን ሠራዊት መሩ። ለመጠባበቂያም ከአድዋ ምዕራብ በኩል በሚገኘው ኮረብታ አፄ ምኒልክ እና እቴጌ ጣይቱ ከራስ ኦሊ እና ዋግሹም ጉዋንጉል አርበኞች ጋር ነበሩ። የኢትዮጵያ ሠራዊትም ራሳቸውን ለአድዋ ሸለቆ ትይዩ የሆነ ኮረብታ ላይ አስቀመጡ።
ከአልቤርቶን ጋር የገጠመው የመጀመርያው ቡድን በራስ መንገሻና በራስ አሉላ ስር የነበረው የትግራይ ሠራዊት ነበረ። እነርሱንም ተቀላቅሎ የንጉስ ተክለ ሐይማኖት፣ የራስ መኮንን እና የራስ ሚካኤል ጦር መጣ፤ ጥቂት ቆይቶም የዋግሹም ጉዋንጉል እና የራስ ኦሊ ጦር መጣ፤ ስለዚህም በአልቤርቶን የተነጠለ የአስካሪ ብርጋዴ ላይ ብዙ የኢትዮጵያ ሠራዊት ተከማቸ። አስቀድሞ የጣልያን ከባድ መሳርያዎች በኢትዮጵያ ሠራዊት ላይ ከፍተኛ ጥቃት አድርሰው ነበር፤ ነገር ግን በባልቻ ሳፎ የተመሩት የኢትዮጵያውያን ክፋዮች ከአባ ገሪማ ተራራ ዝቅተኛ ክፍል ፈጣን ተኳሽ መድፎችን በተኮሱ ጊዜ ነገሩ ተለወጠ። አልቤርቶን እና ጠመንጆቹም ጸጥ አሉ፤ የዚህም ምክንያቱ የአልቤርቶን ተኳሾች በኢትዮጵያ ከባድ መሳርያዎች ተገድለው ስለነበር ነው። የአልቤርቶን በቁጥር የተበለጠ የአስካሪ ጦርም አልቤርቶን እጁን እስኪሰጥ ድረስ ለ2 ሰዓታት ያህል ቦታቸውን ይዘው ቆዩ። የኢትዮጵያም ግፊት ስለነበረባቸው ከአልቤርቶን ሠራዊት ውስጥ የተረፉት በአርሞንዲ ብርጋዴ ውስጥ ለመሸሸግ ወደዱ። የአርሞንዲ ብርጋዴም የኢትዮጵያን ሠራዊት ለ3 ሰዓታት ሲመክት ቆየ፤ ነገር ግን ምኒልክ በእርሳቸው ስር በተጠባባቂነት የተቀመጡትን 25000 ሸዋውያን በለቀቁ ጊዜ የአርሞንዲ ሠራዊት ተሸነፈ።
ጄነራል ባራቴሪም ጦርነቱ ሽንፈት መሆኑን በመገንዘብ ሠራዊቱ እንዲያፈገፍግ አዘዘ። ጄነራሉም በመጠባበቂያ ረድፍ የነበረውን በጄነራል ኤሌና ሥር የሚመራውን ዝግጁ ያልሆነውን ቡድን ሠራዊት እነርሱ በሚያፈገፍጉ ጊዜ እንዲከላከልላቸው ጠየቀ፤ ነገር ግን ከመዋቀራቸው በፊት ሥምሪታቸው እየሸሹ ባሉ የጣልያን ወታደሮች ተሰበረ። የጣልያን ተጠባባቂ ጦርም ጠንካራ መከላከያ የማዋቀር ምንም ዕድል አልነበረውም እናም በደቂቃዎች ውስጥ ተዳከመ።
የዳቦርሚዳ የጣልያን ብርጋዴም አልቤርቶንን ለመደገፍ ተንቀሳቅሶ ነበር፤ ነገር ግን ሊደርስለት አልቻለም። ዳቦርሚዳ ሌሎች የጣልያን ወታደሮች እንደተደመሰሱ አላወቀም ነበር። እርሱም ሠራዊቱ ተከብቦ ተደመሰሰ።
የኢትዮጵያ ፈረሰኞችም በባራቴሪ ስር የነበሩትን የጣልያን ወታደሮች 14 ኪ.ሜ ርቀት ድረስ አሳደዷቸውና ተመለሱ። የሸሹትም የጣልያን ወታደሮች ከ3 ቀን በኋላ የበሌሳ ወንዝን ተሻግረው ወደ ጣልያኗ ኤርትራ ገቡ።
ድልም ለኢትዮጵያ ሆነ!
ዛሬ ድረስ አድዋ በታላቅ ድልነቱ ይታወሳል።
ማጣቀቫ(Reference)
en.m.wikipedia.org/wiki/Battl...
Негізгі бет የአድዋ ጦርነት ታሪክ/The History of the Battle of Adwa/battaglia di Adua
Пікірлер: 5