Egypt: • ስለ ጥንቷ ግብፅ የማታውቋቸው 8 እ...
የኩሽ ግዛት ታሪክ
የከርማ ግዛት በአሁኗ ሱዳን በከርማ ከተማ ማዕከሉን ያደረገ ጥንታዊ ሥልጣኔ ነበረ። ቆይታውም ከክ.ል.በ ከ2500ዓ.ዓ-1500ዓ.ዓ በጥንቷ ኑብያ ነበረ። የከርማ ግዛት መሠረቱ በኑብያ የደቡብ ክፍል ወይም ላየኛው ኑብያ (በአሁኗ ሱዳን ሰሜናዊ እና ማዕከላዊ ክፍሎች ውስጥ) ነበረ እናም ኋላ ላይ ወደ ሰሜን ተስፋፍቶ ወደ ታችኛው ኑብያና የግብፅ ድንበር ድረስ ደርሶ ነበረ። በግብፅ የመካከለኛው ግዛት ወቅት ከርማ በአባይ ሸለቆ ይገኙ ከነበሩ ግዛቶች መካከል አንዱ ነበረ። የከርማ ግዛት የመጨረሻዎቹ ዘመኖች ላይ ማለትም ከ1700ዓ.ዓ-1500ዓ.ዓ ሱዳናዊት ግዛት የነበረችውን ሳይን ጠቅልሎ የተስፋፋና በዛ ያለ ሕዝብ ያለው ግዛት ሆነ፤ ግብፅንም የሚፎካከር ሆነ።
የግብፁ ፈርዖን ቱትሞስ ቀዳማዊም ከግብፅ ወደ ደቡብ ብዙ ዘመቻዎችን አካሄደ። ከክ.ል.በ በ1504ም ኑብያን ጠቀለሉ። ከክ.ል.በ በ1500ም ኑብያ በአዲሷ የግብፅ ግዛት ተጠቀለለች፤ አመፆች ግን ለክፍለ ዘመናት ቀጠሉ። ከርማ ከተያዘች በኋላ የከርማ ባህል ግብፃዊነትን ተላበሰ፤ ግን አመፁ ከክ.ል.በ እስከ 1300ዓ.ዓ ለ220 ዓመታት ያህል ቀጠለ። ምንም ቢሆን ግን ኑብያ በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ እና በመንፈሳዊነት ለግብፃውያን ቁልፍ ክፍለ ሀገር ነበረች። ዋና ፈርዖናዊ ክብረ በዓላት የሚካሄዱትም ለናፓታ ቅርብ በነበረችው በጀበል ባርካል ነበረ። ከክ.ል.በ በ16ተኛው ክፍለ ዘመን በግብፅ ቀኝ ግዛት ስር የነበረችው ኑብያ ወይም ኩሽ የምትመራው ከግብፅ በሚመጣ ምክትል አገረ ገዥ ነበረ።
በሦስተኛው የግብፅ የሽግግር ዘመን ወቅት የግብፅ ዓለም አቀፋዊ ክብር ወደቀ። ታሪካዊ አጋሮቻቸው የነበሩት ከነዓናውያንም በአሶራውያን እጅ ወደቁ። ግብፅም ከክ.ል.በ በ1070ዓ.ዓ በተበታተነች ጊዜ ኩሽ ራሷን የቻለች ግዛት ሆነች።
የኩሽ መሪዎችም የግዛቱን ሐይማኖት ጠባቂና የአማልክቱን ቤቶች የማስተዳደር ኃላፊነት እንዳላቸው ይታሰብ ነበረ። ሰሜናዊቷ ኩሽም ከደቡቢቷ ኩሽ የበለጠ አምራችና ሐብታም ነበረች።
ከክ.ል.በ በ8ተኛው ክፍለ ዘመን አዲስ የኩሽ ግዛት ከናፓታ ተነሳ። የመጀመርያው ናፓታዊ ንጉስ አላራም በኑብያ 25ተኛውን ኩሻዊ ሥርወ መንግስት መሰረተ። አላራ የካዋ መቅደስን ዳግም አስገንብቶ እኅቱን ለአሙን አምልኮ ትኩረቷን እንድታደርግ አስቀመጣት፤ ሌሎች መቅደሶችንም በባካልና በከርማ ዳግም አስገነባ።
የአላራ ተተኪ የነበረው ካሽታም ግዛቱን እስከ ደቡብ ግብፅ እስከ ኤልፋንታይን እና ቲብስ ድረስ አስፋፋው። የካሽታ ተተኪ ፒዬ ደግሞ ከክ.ል.በ በ727ዓ.ዓ የሰሜኗን ግብፅ ተቆጣጠረ። ፒዬ ከ728-716ዓ.ዓ ድረስ ባደረጋቸው ዘመቻዎች የገጠመው ድሎች ምክንያት ያሰራው የድል ሐውልትም በጀበል ባርካል በሚገኘው በአሙን መቅደስ ተገኝቷል። እርሱም ለአራት ግዛት የተከፈለችውን ግብፅ ወረረ።
የፒዬ ተተኪ ሻባታካ ደግሞ ከ711 እና 710ዓ.ዓ መካከል ባለው ጊዜ ውስጥ የሰሜን ግብፅ ነገስታትን አሸንፎ ራሱን በሜምፊስ ንጉስ አድርጎ አስቀመጠ። ከአሶራውያን ንጉስ ከሳርጎን ዳግማዊ ጋርም ህብረት ፈጠረ። ከሻባካ ዘመን በኋላ የነበረው የፈርዖን ቲርሐቅ ሠራዊት ስኬታማ ወታደራዊ ዘመቻዎችን አካሂደዋል። በግብፅ የተያዙት እስያዊ ማኅበረሰቦች በካርናክ በሚገኘው በሙት መቅደስ በተፃፈው መሰረት ሊብያውያን፣ የሻሹ ዘላኖች፣ ፊኖክያኖች እና ፍልስጤሞች ነበሩ። ነገር ግን በደቡብ ልቫንት ሻባታካ ያዝኋቸው ብሎ ያሰባቸው አካባቢዎችን አሶራውያንም የእኛ ናቸው ይሉ ነበረ። ስለዚህም በሜሶፖታምያ ማዕከሉን ባደረገው በአሶር ግዛትና በኩሽ ግዛት መካከል ጦርነት አይቀሬ ሆነ። በ2ተኛ ነገስት 19:9 እና በትንቢተ ኢሳይያስ 37:9 ላይ በተፃፈው መሰረት ከክ.ል.በ በ701ዓ.ዓ ንጉስ ቲርሐቅና ሠራዊቱ ይሁዳን እና ንጉስ ሕዝቅያስን ከአሶራዊው ንጉስ ሰናክሬም ራሳቸውን እንዲከላከሉ ረድቷቸዋል። የአሦራውያን ሠራዊት ኢየሩሳሌም ከተማን መያዝ ለምን እንዳልቻሉ ብዙ መላ ምቶች ይሰጣሉ ከእነዚህም መካከል፦ የቲርሐቅ ሠራዊት፣ በሽታ፣ የመለኮታዊ ጣልቃ ገብነት፣ የሕዝቅያስ እጅ መስጠት ወይም ግብር ለመክፈል መስማማት ይጠቀሳሉ።
የታሪክ አጥኚው ላዝሎ ቶሮክ የግብፅ ሠራዊት በቲርሐቅ ትዕዛዝ ሥር እየተመራ በኤልቴክ እንደተሸነፈ ተናግሯል። ጦርነቱ ግን በሁለቱ ግዛቶች ዘንድ እንደ ድል ተቆጥሯል ምክንያቱም አሦራውያን ኢየሩሳሌምን አልያዙም። ነገር ግን ግብፃውያን እና ኑብያውያን ወደ ግብፅ ተመለሱ። የአሦር ንጉስ ሰናክሬምም የሲናን አካባቢ ያዘ።
የ25ተኛው ሥርወ መንግስት ኃያልነት በቲርሐቅ ጊዜ ከፍታው ላይ ወጥቶ ነበር። የአባይ ሸለቆ ግዛት እንደ ቀድሞው ጊዜ ትልቅ ነበረ። አዲስ ብልፅግና በግብፅ ውስጥ ተነሳ። በሐይማኖት፣ በጥበብ ሥራዎች እና በህንፃ ጥበብ የጥንቱን፣ የመካከለኛውን እና የአዲሱ አሰራር ተመልሷል። የኑብያ ፈርዖኖችም መቅደሶችን እና ሐውልቶችን ሜምፊስ፣ ካርናክ፣ ካዋ እና ጀበል ባርካልን ጨምሮ በጠቅላላው የአባይ ሸለቆ ማስገንባት ወይም መመለስ ጀመሩ። በዚህ በ25ተኛው ሥርወ መንግስት ነበረ በአባይ ሸለቆ ብዙ ፒራሚዶች የተገነቡት፤ በተለይም በአሁኗ ሱዳን። ኩሻውያንም የራሳቸውን የጽሕፈት ሥርዓት አዳበሩ። ፊደሎቻቸውም ሜሮያዊ ፊደላት ይሰኛሉ፤ እነዚህም ከግብፃውያን የጽሕፈት ሥርዓት የተነሱ ናቸው።
ቲርሐቅና የይሑዳዊ አጋሮቹ አስቀድመው ከክ.ል.በ በ674ዓ.ዓ ከአሦርያውያን ጋር በአስቀሎና ጦርነት ገጥመው አሸንፈዋቸው ነበረ። አንፃራዊ በሆነ ሁኔታ ትንሽ የነበረው የአሦራውያን ጦር አስቀድሞ በአካባቢው የሚገኙትን ከነዓናውያንን እና የአረብ ጎሳዎችን አሸንፈው ነበረ፤ ከዛም በታላቅ ፍጥነት ወደ አስቀሎና በዘመቱ ጊዜ ተዳክመው ነበረ። ነገር ግን በ671ዓ.ዓ የአሦር ንጉስ አስራዶን በዛ ያለና ይበልጥ የተዘጋጀ ሠራዊት አዋቅሮ በግብፅ ላይ ዘመቻ ከፈተ። አሦራውያንም በፍጥነትና ወሳኝ በሆነ ሁኔታ ግብፅን እየተቆጣጠሩ ሄዱ። ሜምፊስ ተያዘች፤ ቲርሐቅም ወደ ኑብያ ሸሸ፤ ነገር ግን የቲርሐቅ ተተኪውና ሌሎች የቤተሰብ አባላቱ ወደ አሦር ግዛት ዋና ከተማ ወደ ነነዌ በምርኮ ተወሰዱ። አስራዶንም ሁሉንም ኩሻዊ ከግብፅ ምድር በማስወጣቱ ጎረረ። ነገር ግን አስራዶን በግብፅ ግብፃውያንን የክፍለ ሀገር መሪ አድርጎ ከእርሱ በታች እንደ አሻንጉሊት እንዲቀመጡ አደረጋቸው። ቲርሐቅም ተመልሶ ሜምፊስን ተቆጣጠረ። ከክ.ል.በ በ669ዓ.ዓ አስራዶን ዳግም ቲርሐቅን ከግብፅ ለማስወጣት በሚጓዝበት ጊዜ በመንገድ ሳለ ግብፅ ሳይደርስ በሀራን ሞተ፤ ይህም ስራው በተተኪው በአሱርባኒፓል እንዲቀጥል አደረገው። እርሱም ቲርሐቅን አሸነፈው፤ ቲርሐቅም ዳግም ወደ ኑብያ ሸሸ። ቲርሐቅም ከክ.ል.በ በ664ዓ.ዓ በናፓታ ሞተ።
የቲርሐቅ ተተኪ ታንታማኒም ከብዙ ሠራዊት ጋር ከናፓታ ተነስቶ ወደ ሰሜን በኤልፋንታይን በኩል ወደ ቲብስ ሄደ፤ በዛም በመንፈሳዊ ሥርዓት የግብፅ ንጉስ ተደርጎ ተሾመ። ከቲብስም ታንታማኒ በአሦርያውያን እንደ አሻንጉሊት ከተቀመጡት መሪዎች እጅ ሙሉ ግብፅን እስከ ሜምፊስ ድረስ ዳግም ለመውሰድ ሙከራውን ጀመረ። ሳዮችን ካሸነፈና በአሦር ሜምፊስን ያስተዳድር ዘንድ የተሾመውን ኔኮ ቀዳማዊን ከገደለ በኋላ አንዳንድ ሥርወ መንግስታት ለእርሱ ተገዙ፤ ሌሎች ደግሞ ወደ ምሽጎቻቸው ሸሹ። አሦራውያንም ከክ.ል.በ በ663ዓ.ዓ ብዙ ሠራዊት ወደ ደቡብ ላኩ። ታንታማኒ ተከበበ፤ የአሦር ሠራዊትም ቲብስን አወደሙ፤ ውድመቱም ከፍተኛ ስለነበረ ከዛ ወዲህ ቲብስ አላገገመችም። ታንታማኒንም ወደ ኑብያ አባረሩት፤ ነገር ግን በደቡብ ግብፅ ቦታ ለመያዝ ከክ.ል.በ እስከ 656ዓ.ዓ ድረስ ሲታገል ቆየ። በኩሽ እና በደቡብ ግብፅ መካከል ያለው የመጨረሻው ሕብረት ከክ.ል.በ በ590ዎቹ ከሳይት ነገስታት ጋር በነበረው ግጭት ምክንያት ተቋረጠ።
ከክ.ል.በ በ530ዓ.ዓ የፋርስ ንጉስ ካምባሲስ ኩሽን እንደወረረ ግሪካዊው ታሪክ አጥኚ ሄሮዳተስ ዘግቧል፤ ነገር ግን ሄሮዳተስ እንዳለው ከሆነ ፋርሶች ከፍተኛ በሆነ ሁኔታ በበረሃ ተሸንፈዋል።
ኩሽም ከግብጿ ሮም ጋር ተደጋጋሚ ጦርነት በማድረጓ ምክንያት ከክ.ል.በኋላ በመጀመርያውና በሁለተኛው ክፍለ ዘመን ኃይሏ እየተዳከመ ሄደ። መዳከሟም በቀጠለ ጊዜ በግዛቱ ውስጥ ብዙ አመፆች ተነሱ። በ4ተኛው ክፍለ ዘመን መሃል ላይ ኩሽ አክሱም ላይ ጦርነት ከፈተች፤ የዚህም ምክንያቱ በዝኆን ጥርስ ንግድ ምክንያት በተፈጠረ ግጭት ነው። አክሱምም በንጉስ ኢዛና ጊዜ ብዙ ጦር ይዛ ሄዳ ሜሮይን አፈረሰች፤ የኩሽ ሥልጣኔም ፈረሰ። በዛም ክርስትና በጥንት ፈርዖናዊ ሐይማኖት ላይ የበላይነት ያዘ፤ በ6ተኛው ክፍለ ዘመን መሐል ላይም የኩሽ ሥልጣኔ ጠፋች።
ማጣቀሻ(Reference)
en.m.wikipedia.org/wiki/Kingd...
#adwa #christianity #ethiopia #ethiopianhistory #ethiopianorthodox #history #religion #sultanate #ታሪክ #africa #nubia #kush #egypt #rome #royal #meroe #assyrian
Негізгі бет የኩሽ ግዛት ታሪክ/The history of Kingdom of Kush በአክሱም የተወረረችው ግዛት ኑብያ
Пікірлер: 6