ትውልድ፡ እድገት እና ትምህርት
------
ወጋየሁ ግንቦት 28 ቀን 1936 ዓ.ም አዲስ አበባ ቀበና ነው የተወለደው። ወላጅ አባቱ አቶ ወጋየሁ ብዙነህ፣ ወላጅ እናቱ ወ/ሮ አምሳለ በየነ ይባላሉ። አባትና እናቱን ያጣው ገና በልጅነቱ ነበር፣ ወንድምና እህትም አልነበረውም። ብቸኛ ልጅ ነበር ወጋየሁ ለቤተሰቦቹ። የስለት ልጅ!
ወጋየሁ በ1942 ዓ.ም. አካባቢ አቃቂ በሚገኘው የስዊድን ወንጌላዊት ሚሲዮን ት/ቤት ትምህርቱን ጀመረ። የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱን እንደጨረሰ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ በዳግማዊ ምኒልክ እና በተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤቶች ተከታተለ፡፡ ወጋየሁ በት/ቤት ቆይታው በአንዳንድ የተለዩ አጋጣሚዎች የተሰጥኦ ትርዒት ያቀርብ ነበር፡፡ ከተሰጥኦ ትርዒቶቹ ዋናው የልዩ ልዩ እንስሳትን ድምፅ አስመስሎ ያወጣው የነበረው ይጠቀሳል።
በ1955 ዓ.ም. የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ ቀደም ሲል የአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ አቋቁሞት በነበረው “ኪነ ጥበብ ወትያቲር” ይባል ወደነበረው የአሁኑ የባህል ማዕከል በመግባት ከጓደኞቹ ከአባተ መኩሪያ እና ደበበ እሸቱ ጋር እንቅስቃሴ ማድረግ ጀመረ:: በወቅቱ የማዕከሉ ኃላፊ በነበሩት ፍሊፕ ካፕላን አማካኝነትም የትወናን፣ የዝግጅትንና የፅህፈተ-ተውኔትን መሠረታዊ እውቀት ተማረ።
ወጋየሁና የጥበብ አበርክቶው
-----
ወጋየሁ ትያትርን የኖራት፣ ያከበራትና ያስከበራት ድንቅ ልጇ ነበር። በነጋሽ ገብረማርያም “የድል አጥቢያ አርበኛ” እና “የአዛውንቶች ክበብ” ፤ በመንግስቱ ለማ “ፀረ ኮሎኒያሊስት” ፣ በፀጋዬ ገብረ መድህን “እናት ዓለም ጠኑ” እና “ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት” ፣ በመላኩ አሻግሬ “አንድ ጡት” ፣ በማሞ ውድነህ “አሉላ አባነጋ” ፣ በተስፋዬ ገሠሠ “ፍርዱ ለእናንተ” ወዘተ. ቴያትሮች ውስጥ መልኩን እየለዋወጠ በተጫወታቸው ገፀባሕሪያት ወጋየሁ ነፍሱና ስጋው ለትያትር ጥበብ መፈጠሯን ማስመስቀር የቻለ የትያትር እንቁ ነበር።
ዘነበ አብርሃ “የመድረኩ ኮከብ” በተሰኘ ርዕስ ስለ ወጋየሁ ንጋቱ ሲጽፍ “ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁትም ቀልቤን የወሰደውም የታዋቂውን ባለቅኔ የፀጋዬ ገ/መድህንን “ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት” ቴያትር ሲሰራ ነው። ወጣትነቱም አይሎ ነው መሰል ዕንባዬን መግታት ተሳነኝ። ደግነቱ አዳራሹን የሞላው ታዳሚ ሁሉ ይነፈርቃል” በማለት ወጋየሁ በአቡነ ጴጥሮስ ተመስሎ ሲጫወት የፈጠረበትን ስሜት ይገልጻል። ወጋየሁ እንደዚህ ነው! መስሎ ሳይሆን ሆኖ ነው የሚሰራው። የሱን ትያትሮች በመድረክ ላይ የመታደም እድል ያገኙ የትያትር ተመልካቾች በአንድ ድምጽ የሚመሰክሩትም እውነት ይሄው ነው። ወጋየሁ መሆን እንጂ መምሰልን፣ ማስመሰልን አያውቅበትም።
ወጋየሁ ንጋቱ እንዴት የተዋጣለት ተዋናይ ሊሆን እንደቻለ “ዜና ቱሪዝም” በአንድ ወቅት ላቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ “… የስቴጅ ዓይኔን የከፈተው … ተስፋዬ ገሠሠ ነበር። የድራማ መምህሬ፤ የተውኔት አባቴ እርሱ ነው” ሲል መልሷል። ይህን ውለታዉንም ሳይረሳ እሱም ያለውን እውቀትና ክህሎት ለሌሎች ተተኪ ባለሞያዎች በማስተማር እና በማካፈል የወጣት ባለሞያዎችን የስቴጅ ዓይን በመክፈት መልሷል። ወጋየሁ በ1967፣ በ1969 እና በ1970 ዓ.ም. ብሔራዊ ቴያትር በሰጠው የተዋንያን ሥልጠና አስተማሪ በመሆን የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ አበርክቷል። ከተማሪዎቹ ውስጥ እነሲራክ ታደሰ፣ ዓለምፀሐይ ወዳጆ፣ ተክሌ ደስታ፣ መዓዛ ብሩ፣ ዓለምፀሐይ በቀለ፣ ዓይናለም ተስፋዬ፣ ኃይሉ ብሩና የመሳሰሉት ይገኙበታል።
ወጋየሁ የቲያትር ሙያ እውቀቱን ለማጉልበትም ከፍተኛ ጥረት ያደርግ ነበር። በ1959 ዓ.ም. ከደበበ እሸቱ ጋር ወደ ሀንጋሪ ቡዳፔስት ተልኮ የሥነ-ተውኔት ሙያን ለሁለት ዓመታት አጥንቶ ተመለሰ። ከሀንጋሪ እንደተመለሰ በሬዲዮና በቴሌቪዥን አጫጭር ተውኔቶችን ማቅረብ ቀጠለ። በተለይም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ለተመልካች እንግዳ የሆኑ አስማተኛው፣ ቁንጫ፣ አባሉን፣ ቀለም ቀቢው፣ የተዘጋ በር እና የመሳሰሉ ድምፅ አልባ (ማይም ተውኔቶችን ማቅረብ በመጀመሩ ተደናቂነትን እያተረፈ መጣ፡፡ በ1962 ዓ.ም. በሀገር ፍቅር ቲያትር ቤት ተቀጠረ። የቲያትር ክፍሉ ኃላፊ፣ አዘጋጅ፣ ተዋናይና እንዲሁም በሙያው ለመስራት የሚፈልጉ ወጣቶችን በማስተማር ሁለገብ አገልግሎትን ሰጥቷል።
ከዚህ በኋላ ወደኢትዮጵያ ሬዲዮ ተዛወረና ለመዝናኛ ፕሮግራም አቅራቢነትና በዜና አንባቢነት ሲሰራ ቆየ። በዚህ ሥራ ለአራት ዓመታት አገልግሎ በብሄራዊ ቲያትር ቤት ተቀጠረ፡፡ በብሄራዊ ቲያትር ቤት ከተቀጠረበት ጊዜ አንስቶም ቀጥሎ በተዘረዘሩት ተውኔቶች አብይ ሚናዎች እየወከለ ተጫ ውቷል፡፡
ትግላችን፣
የስጋ ሌሊት ራዕይ ፣
ደማችን፣
ደመ መራራ፣
ሞረሽ፣
ሀሁ በስድስት ወር፣
ፀረ-ኰሎኒያሊስት፣
አፅም በየገፁ፣
እናት ዓለም ጠኑ፣
የአዛውንቶች ክበብ፣
ዋናው ተቆጣጣሪ፣
ፍርዱን ለእናንተ፣
ጴጥሮስ ያቺን ሰዓት፣
ክራር ሲከር፣
ሀምሌት፣
ሊየር ነጋሲ፣
የድል አጥቢያ አርበኛ፣
ዘርዓይ ደረስ፣
ገሞራው፣
አሉላ አባነጋና
እናት ነሽ ናቸው፡፡
ከነዚህ ተውኔቶች በአንዳንዶቹ በዋና አዘጋጅነትና በተዋናይነትም ሰርቷል።
ወጋየሁ እና ፍቅር እስከ መቃብር
-----
ወጋየሁ ንጋቱ ከሚታወቅባቸው ተግባራቱ አንደኛው በሬዲዮ ያቀርብ የነበረው የመፅሃፍት ትረካ ነው። በመፅሃፍት ዓለም ፕሮግራም በሬዲዮ ከተረካቸውና ኣድናቆትን ካተረፉለት መፅሃፍት መካከል የሀዲስ አለማየሁ ፍቅር እስከ መቃብር፣ የብርሃኑ ዘሪሁን ሶስት መፅሃት ማዕበል የአብዮት ዋዜማ፣ ማዕበል የአብዮት መባቻ እና ማዕበል የአብዮት ማግስት የተባሉትና የገበየሁ አየለ ጣምራ ጦር ከተደራሲያን አዕምሮ የማይጠፉ ናቸው። ያም ሆኖ ግን እንደ ፍቅር እስከ መቃብር የወጋየሁ ንጋቱ የሬዲዮ ትረካ ችሎታው ነጥሮ የወጣበት እና ዛሬም ድረስ ተወዳጅ የሆነበት ስራ ያለ አይመስልም። ለዚህ ድንቅ ስራው የመጽሀፉ ደራሲ አዲስ አለማየሁ መፅሃፋቸው ተተርኮ እንዳለቀ ለወጋየሁ “እኔ ከፃፍኩት ይልቅ አንተ በህዝቡ ኣዕምሮ የሳልከው ይበልጣል” የሚል የአድናቆት አስተያየት ሰጥተውታል፡፡
አንጋፋው ከያኒ ወጋየሁ ንጋቱ በሕይወት ዘመኑ በመድረክ 30፣ በቴሌቪዥን 18፣ በሬዲዮ 46 በጠቅላላ 94 ቴያትሮችን በመጫወትና የህዝብ ልጅ በመሆን ዘመኑን አልፏል።
ሰአሊ እሸቱ ጥሩነህ ‹‹መላ አካሉ ቋንቋው›› በሚል ርዕስ የወጋየሁ የሰውነት፣ የቁመት፣ የፊት፣ ቅርጽ ሁኔታ ላይ ጠለቅ ያለ ሂሳዊ ጽሁፍ አቅርበዋል። ታዋቂው ሀያሲ ስዩም ወልዴም ‹‹ገጸ ብዙ ጠቢብ›› ብሎ የወጋየሁን ሁለገብ የተዋናይነት ብቃት አብራርቶ ጽፏል።
ረዳት ፕሮፌሰር ሀይማኖት ዓለሙ ወጋየሁ ለመድረክ የተፈጠረ መሆኑን መስክረዋል። አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም በበኩሉ ወጋየሁ ከእርሱ በኋላ ለሚመጡ ተዋናዮች እውቀቱን ለማካፈል ፍጹም የማይሳሳ እነደነበር ተናግሯል።
ወጋየሁ በ1966 ዓ.ም እንደ ፀረ-አብዮተኛ ተቆጥሮ ለጥቂት ጊዜያት ታስሮ ተፈትቷል፡፡ በ1977 ዓ.ም. ከባህል ሚኒስቴር ሠራተኞች መካከል ‹‹ምሥጉን ሠራተኛ›› ተብሎ ተሸልሟል፡፡
ወጋየሁ ወደመጨረሻው የህይወት ዘመኑ በግልፅ አውጥቶ በማይናገራቸው ጉዳዮች ይበሳጭ እንደነበርና አብዝቶ የመጠጣት ችግርም አጋጥሞት እንደነበር ይነገራል። በመጨረሻም ኅዳር 6 ቀን 1982 ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ።
ለተጨማሪ ፅሁፎች የሰዋስው መተግበሪያዎችን ያውርዱ ወይም ድረ ገፃችንን ይጎብኙ!
sewasew.page.l...
#ወጋየሁ #ንጋቱ #ቴያትር #ጥበብ #ታሪክ #ታዋቂሰዎች #አፍሪካ #ኢትዮጵያ #Wegayehu #Nigatu #Theater #Art #History #Personalities #Africa #Ethiopia
Негізгі бет የመድረኩ ጌታ ወጋየሁ ንጋቱ (Wegayehu Nigatu)
Пікірлер: 7