ማቴ. ፳፬፥፬‐፶፩
እንኳን ለክብር ባለቤት ለጌታችን ለአምላካችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ከዘጠኙ ንዑስ በዓላት አንዱ ለሆነው ለዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ለደብረ ዘይት እግዚአብሔር በሰላም በጤና አደረሰን።
የደብረ ዘይት መዝሙር፦
"እንዘ ይነብር እግዚእነ ውስተ ደብረ ዘይት ወይቤሎሙ ለአርዲኢሁ ዑቁኬ ኢያስሕቱክሙ ወንበሩ ድልዋኒክሙ ብዙኃን ይመጽኡ በስምየ እንዘ ይብሉ አነ ውእቱ ክርስቶስ ወዘአዝለፈ ትዕግሥቶ ውእቱ ይድኅን ወአመ ምጽአቱሰ ለወልደ እጓለ እመሕያው ይትከወስ ኵሉ ኀይለ ሰማያት ወምድር አሜሃ ይበክዩ ኵሎሙ ኀጥአነ ምድር። ወይወርድ እግዚእነ እምሰማይ ዲበ ምድር በትእዛዙ ወበቃሉ ወበአዕላፍ መላእክቲሁ በንፍሐተ ቀርን ዘእምኀበ እግዚአብሔር ይምሐረነ አብ በይእቲ ሰዓት እሞተ ኃጢአት እስመ ገባሬ ሕይወት ውእቱ እግዚአ ለሰንበት። ትርጉም፦ ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ተቀምጦ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፤ ተዘጋጅታችሁም ኑሩ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ እስከ መጨረሻው የጸና እርሱ ይድናል። የሰው ልጅ በሚመጣበት ጊዜ የሰማያትና የምድር ኃይላት ሁሉ ይናወጣሉ። ያን ጊዜ በምድር ኃጢአት ያደረጉ ሁሉ ያለቅሳሉ አላቸው። ጌታችንም ከባሕርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ በመለከት ድምጽ ከአእላፍ መላእክት ጋር በግርማ መለኮቱ ከሰማይ ወደ ምድር ይወርዳል። በዚች ዕለት ሞትን ከሚያስከትል ኃጢአት አብ ይማረን የሕይወት ባለቤት የሰንበትም ጌታ ነውና። ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በድጓው ላይ።
ደብረ ዘይት
የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት ይባላል ፡፡ ደብረ ዘይት ማለት የወይራ ዛፍ የበዛበት ተራራ ማለት ነው ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌ በዚህ ዓለም እየተዘዋወረ በሚያስተምርበት ሰዓት ከቅዱሳን ሐዋርያት ስለ ዓለም ፍፃሜ ምልክቶች የቀረበለትን ጥያቄ አስመልክቶ መልስ የሰጠበትን ዕለት በማስታወስ የሚከበር እሁድ “ እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው ። ንገረን ይህ መቼ ይሆናል ? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው ? አሉት ። ” ማቴ. ፳፬፥፫ ይህንን ሥርዓት የሰራው ደግሞ ታላቁ የቤተ ክርስቲያን የዜማ አባት ቅዱስ ያሬድ ነው ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የዓለም ፍፃሜ መድረስ አስመልክተው የሚታዩ ምልክቶችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ነግሯቸዋል ፡፡ “ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ ። ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና ብዙዎችንም ያስታሉ ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ አትደንግጡ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው .… የዚያ ባሪያ ጌታ ባልጠበቃት ቀን ባላወቃትም ሰዓት ይመጣል ከሁለትም ይሰነጥቀዋል እድሉንም ከግብዞች ጋር ያደርግበታል በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል"። ማቴ. ፳፬፥፬‐፶፩
የዕለቱ ምስባክ፦
"እግዚአብሔርሰ ገሀደ ይመጽእ።
ወአምላክነሂ ኢያረምም"።
እሳት ይነድድ ቅድሜሁ። መዝ 49፥3።
የሚነበቡት መልዕክታት
1ኛ ተሰ 4፥13-ፍ.ም፣
2ኛ ጴጥ 3፥7-15 እና የሐዋ ሥራ 24፥1-22።
የሚነበበው ወንጌል ማቴ 24፥1-36። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ አትናቴዎስ ቅዳሴ ነው። መልካም የደብረ ዘይት በዓል።
Негізгі бет #ሊቀ
Пікірлер